Ezk 15

? AI
1
የእግዚአብሔርም ቃል ወደ እኔ እንዲህ ሲል መጣ።
2
የሰው ልጅ ሆይ፥ የወይን ግንድ፥ በዱር ዛፎች መካከል ያለ የወይን አረግ፥ ከዛፍ ሁሉ ይልቅ ብልጫው ምንድር ነው?
3
በውኑ ሥራ የሚሠራበትን እንጨት ከእርሱ ይወስዳሉን? ወይስ ሰዎች ዕቃ የሚንጠለጠልበትን ኵላብ ከእርሱ ይወስዳሉን?
4
እነሆ፥ ለመቃጠል በእሳት ላይ ተጥሎአል፥ እሳቱም ሁለቱን ጫፎቹን በልቶአል፥ መካከሉም ተቃጥሎአል፤ በውኑ ለሥራ ይጠቅማልን?
5
እነሆ፥ ደህና ሳለ ለሥራ ካልጠቀመ፥ ይልቁንስ እሳት ከበላው እርሱም ከተቃጠለ በኋላ እንዴት ሥራ ይሠራበታል?
6
ስለዚህ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል። በዱር ዛፎች መካከል ያለውን የወይን ግንድ እሳት ይበላው ዘንድ እንደ ሰጠሁት፥ እንዲሁ በኢየሩሳሌም የሚኖሩትን አሳልፌ እሰጣለሁ።
7
ፊቴንም በእነርሱ ላይ አደርጋለሁ፤ ከእሳትም ይወጣሉ፥ እሳት ግን ይበላቸዋል፤ ፊቴንም በእነርሱ ላይ ባደረግሁ ጊዜ እኔ እግዚአብሔር እንደ ሆንሁ ታውቃላችሁ።
8
ዓመፅን አድርገዋልና ምድሪቱን ባድማ አደርጋለሁ፥ ይላል ጌታ እግዚአብሔር።
Global Bible Tools - Collaborative Bible translation platform